Wednesday, June 30, 2010

ዝምታ ወርቅ አይደለም

የርሶ ብዕር አስተያየት ተሳትፎ ሕብረተሰባችንን ይጠቅማል ያሉትን አይንፈጉን ገንቢነቱ ቦታ ይኖረዋልና!


ማሳሰቢያ፡ ይህ ገጽ የተዘጋጀው የተለያዩ የኅብረተሰባችንን ሀሳብ ለመለዋወጫ እንጂ ለሚሰጡት ማንኛውም አስታየቶች በማንኛውም መንገድ ተጠያቂ አይደለም። ጉግል ድርጅትም ኃላፊነት አይወስድም። ኃላፊነቱ በሙሉ የአስታየት ሰጪው ብቻ ነው።





እንደምን አላችሁ?



የሚቀጥለውን ጽሁፍ የቸሩንን ታዳሚያችን ከልብ ምስጋና ይድረሳቸው፣ ብዙዎቻችን ከዚህ በፊት አንበነው ይሆናል ግን ምን ያህል ተረድተነው ይሆን? ለማንኛውም ደግመን በማስተዋል እናነበው ዘንድ እንጋብዛለን።



ዝምታ ወርቅ አይደለም





ሰውዬው ከሚስቱ ሌላ አንዲት ሴት ወደደና እፍ ክንፍ አለ፡፡ ልጁን እና ሚስቱን እየተወ ከዚህችኛይቱ ጋር ማምሸት፣ ብሎም ማደር ጀመረ፡፡ በመጨረሻም አንድ ቀን ወደ ሚስቱ መጣና ድንገተኛ የሆነ ጥያቄ አቀረበ፡፡ «እኔ እና አንቺ እንድንፋታ እፈልጋለሁ፤ ለምን ብለሽ ምክንያቱን አትጠይቂኝ፡፡ መፋታት ብቻ እፈልጋለሁ፡፡ ደግሞም ሌላ ቀን አይደለም፣ ነገ እንዲሆን እፈልጋለሁ» አላት፡፡ ሚስቱ በሁለት ነገሮች ተጨነቀች፡፡ በአንድ በኩል ምንም ነገር አትጠይቂኝ ብሏታል፡፡ በሁለተኛ ነገር ልጇ ወደ ዩኒቨርሲቲ የመግቢያ ፈተና ልትቀመጥ ጥቂት ቀናት ቀርቷታል፡፡



«ባልፈልገውም፣ ባልስማማበትም፤ ካልክ የግድ እቀበለዋለሁ፡፡ ነገር ግን በኛ ምክንያት ልጃችን መጎዳት የለባትምና የአንድ ወር ጊዜ ያህል እንታገሥ፡፡» አለችው፡፡ እርሱም አሰበና «ጥሩ አንድ ወር መታገሥ አያቅተኝም፤ ነገር ግን በዚህ አንድ ወር ውስጥ ሽማግሌ መላክ፣ ምክንያቱን መጠየቅ የለም፤ ስለ ፍቺው ማናችንም ምንም ነገር ማንሣት የለብንም፤ በዚህ ቃል ግቢ» አላት፡፡ እርሷም «እስማማለሁ፤ ግን አንተም የምነግርህን ለመፈጸም ከተስማማህ ነው፤ ታድያ በዚህ አንድ ወር ጠዋት ጠዋት ከዕንቅልፌ ስነሣ፣ ማታ ማታም ወደ አልጋዬ ስሄድ ያኔ የሠርጋችን ዕለት አቅፈህ እንደ ወሰድከኝ አድርገህ አቅፈህ ትወስደኛለህ» ስትል ጠየቀችው፡፡ ነገሩ ያልጠበቀው እና ያልተለመደ ዓይነት ቢሆንበትም፣ ቀላል እና ሊያደርገው የሚችል ስለሆነ እሽ ብሎ ቃል ገባላት፡፡



አንዱ ወር ተጀመረ፡፡



ጠዋት ጠዋት ከዕንቅልፏ ስትነሣ አቅፎ፣ ከፍ አድርጎ፣ ወደ በረንዳ ካደረሳት በኋላ ወደ ሥራው ይሄዳል፡፡ ማታ ማታም እንዲሁ አቅፎ ወደ አልጋዋ ይወስዳታል፡፡ ስለ ፍችው አይነጋገሩም፡፡ እየዋለ እያደረ ሲሄድ የሰውነቷ ጠረን፣ የምትለብሳቸው ልብሶቿ፣ የዓይኖቿ እና የፀጉሯ ሁኔታ፣ የገላዋ ልስላሴ እና የአካሏ ቅርጽ እየሳቡት መጡ፡፡ በየቀኑ እያቀፈ ሲያወጣት እና ሲያስገባት ሰውነቷ እየቀለለው፤ ለርሱም እርሷን አቅፎ መሸከሙ አንዳች እንግዳ የሆነ የደስታ ስሜት እየፈጠረለት መጣ፡፡



ከራሱም ጋር ሙግት ጀመረ፡፡ «ለምንድን ነው እንፋታ ያልኳት፤ አሁን የሚሰማኝን ስሜት ያህል ስሜት ከአዲሷ ወዳጄ ጋር ለምን አይሰማኝም? ለምንስ ነበር ይህንን ነገር እንዳደርገው ቃል ያስገባችኝ ? ይህን የመሰለውን ገላዋን፣ እንዲህ የሚማርከውን ጠረንዋን፣ እንዲህ የሚያስደስተውን ፈገግታዋን፣ እንዲህ የተዘናፈለውን ፀጉሯን፣ እንዲህ ልዩ የሆነውን አካሏን እንዴት እስከ ዛሬ አላስተዋልኩትም ?እርሷ ናት ከኔ ጋር የነበረችው ወይስ እኔም ከርሷ ጋር ነበርኩ?»



የወሩ መጨረሻ እየደረሰ መሆኑን ሲያውቅ ከእርሷ መለየቱ ጨነቀው፡፡ እንዲያውም ይህ ሁኔታ የፈጠረበትን እንግዳ ስሜት እየወደደው መጣ፡፡ ነግቶ እና መሽቶ እርሷን አቅፏት እስከሚወስዳት በጉጉት መጠበቅ ጀመረ፡፡ በሌላም በኩል ደግሞ በዚህ ድርጊቷ በውስጡ ያሳደረችበትን ስሜት እያሰበ ያደንቃትም ጀመር፡፡ ብልህነቷን፣ አስተዋይነቷን እና በቀላል ድርጊት ቀልቡን ልትገዛው መቻሏን ሲያስበው «ምን ዓይነት አስገራሚ ሴት ናት?» ይላል፡፡



ወሩ ሊያልቅ ሁለት ቀን ሲቀረው የመፋታቱን ሃሳብ በውስጡ መረመረው፡፡ ነገር ግን አላገኘውም፡፡ በዚህ ሁኔታ መፋታቱ ደግሞ ለሕይወቱ የማይፈታ ዕንቆቅልሽ እንደሚሆንበት እያሰበ ተጨነቀ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ በዚህ አንድ ወር ውስጥ ፍችን በተመለከተ ላለመነጋገር ቃል ተግባብተዋልና እንዴት አድርጎ ይናገር፡፡ ዛሬም በደስታ ስሜት አቅፎ ከአልጋዋ እንደወሰዳት ሁሉ ማታ ወደ አልጋዋ መለሳት፤ ከበፊቱ እጅግ በጣም ቀለለችው፤ አሳዘነችውም፡፡



በወሩ መጨረሻ፡፡



ወደ አዲሲቱ ወዳጁ ዘንድ ሄደና «የፍችውን ሃሳብ ሠርዤዋለሁ፡፡ እኔና ባለቤቴ ፍቅር የሌለን መስሎኝ ነበር፡፡ እኛ ግን ለካስ ፍቅር አላጣንም፡፡ ያጣነው ሁለት ነገሮች ብቻ ነው፡፡ መነጋገር እና መቀራረብ፡፡ ለዚህ ያደረሰንም አለ መቀራረባችን እና አለመነጋገራችን ብቻ ነው፡፡ አሁን ግን መነጋገር ባንችል እንኳን መቀራረብ ግን ችለናል፡፡ ዛሬ ደግሞ መነጋገር እንችላለን፡፡ ስለዚህ ሌላ የሚሆንሽን ፈልጊ» አላት፡፡



ሴትዮዋ ተናደደችና በጥፊ መታችው፤ ከአጠገቧ የነበረውንም ውኃ ቸለሰችበት፤ «ይሄ ለብዙው ኃጢአቴ የተከፈለ ቅጣት ነው» እያለ ወጥቶ ሄደ፡፡ ከዚያም ወደ አበባ መሸጫ ሱቅ ውስጥ ገባ፡፡ ያኔ ሲጋቡ የገዛላትን ዓይነት አበባ ገዝቶ ወደ ቤቱ ከነፈ፡፡ «ጓደኛዬ ትዳር ማለት አግብተው የሚኖሩት ሳይሆን በየጊዜው የሚጋቡት ነው ያለው እውነቱን ነው፡፡ ትዳር እንደ አሥራ ሁለተኛ ክፍል ፈተና አንድ ጊዜ አልፈውት ሰርተፊኬቱን የሚሰቅሉት አይደለም ያለው እውነቱን ነው፡፡ ትዳር እና ተክል ክብካቤ ይፈልጋሉ፡፡ እንዲሁ ቢያድጉ ይደጉ ተብለው የሚተው ነገሮች አይደሉም፡፡



«ልክ እዚህ ሀገር ችግኝ የመኮትኮት፣ የማጠጣት፣ የመከባከብ እና የማሳደግ እንጂ የመትከል ችግር እንደሌለብን ሁሉ፤ እኛም ጋር የመጋባት ችግር የለም፡፡ ፍቅር ግን ማግባትን ብቻ ሳይሆን ማጠጣትን፣ መኮትኮትን፣ ማረምን፣ ከብት እንዳያበላሸው አጥር ማጠርን፣ በየጊዜው ማዳበርያ መጨመርን ጭምር ይፈልጋል፡፡ በርግጥ በዕድሉ የሚበቅል ዛፍ እንዳለው ሁሉ በእድሉ የሚኖር ትዳርም ይኖር ይሆናል፡፡ ይህ ግን ሕይወትን ለራስ ጥረት ሳይሆን ለአጋጣሚዎች ብቻ አሳልፎ መስጠት ነው» ያለው እውነቱን ነው፡፡ እኔ አልሰማሁትም እንጂ እርሱስ ተናግሮ ነበር፡፡»



መኪናውን አቆመና ወደ ግቢው ውስጥ ገባ፡፡ በረንዳ ላይ ትጠብቀው የነበረችው ባለቤቱ የለችም፡፡ በሩንም አንኳኳ፡፡ የሚከፍት ግን አልነበረም፡፡ ደግሞ ሲያንኳኳ ገርበብ ብሎ የተዘጋው በር በራሱ ጊዜ ተከፈተ፡፡ ባለቤቱ ግን በዚህች በወሩ ሠላሳኛ ቀን ሳሎንም የለችም፡፡ እየተገረመም፣ ግራ እየተጋባም ወደ መኝታ ቤቱ ዘለቀ፡፡ አልጋው ላይ ፈገግ እንዳለች ጋደም ብላለች፡፡ አበባውን እንደያዘ ጠጋ አለና በእጁ ጉንጯን ነካው፡፡ ቀዝቅዟል፡፡ በቁልምጫ ጠራት፡፡ መልስ ግን አልነበረም፡፡ ግራ ተጋብቶ ዓይንዋን ገለጥ አደረ ገው፡፡ ሊገለጥለት ግን አልቻለም፤ በርከክ አለና ሰውነቷን ደባበሰው፤ ቀዝቅዟል፡፡



«የመጨረሻው ቀን ነው፤ ይህችን ቀን ማየት አልፈልግም፤ ለልጄ ስል እስከዛሬ ታግሻለሁ፤ በቃኝ» የሚል ጽሑፍ ራስጌዋ ላይ አገኘ፡፡



እርሷ ፍችውን አትፈልገውም፤ ስለዚህም ሳትፋታ ሞተች፡፡ በርሱ ውስጥ የነበረውን የሃሳብ ለውጥ አላወቀችም፤ ምክንያቱም ላይነጋገሩ ቃል ተግባብተው ነበርና፡፡ እርሷ የዛሬዋን ቀን በስጋት እና በጭንቀት ነበር የጠበቀቻት፡፡ የመለያያቸው ቀን፤ የሕይወቷን ግማሽ የምታጣበት ቀን፡፡ የማትፈልገውን ነገር የምታደ ርግበት ቀን ናትና፡፡ እርሱ ግን የዛሬዋን ቀን በጉጉት ነበር የጠበቃት፡፡ የሚነጋገሩባት ቀን፤ ፍችውን እንደተወው የሚነግርባት ቀን፤ ፍቅሩን የሚነግርባት ቀን፤ ይቅርታ የሚጠይቅባት ቀን፤ ለፍቅሩ ሲል ትንሽም ብትሆን ቅጣት ከፍሎ የመጣባት ቀን፤ በእርሱ እና በባለቤቱ መካከል የመነጋገር እና የመቀራረብ እንጂ፣ የመዋደድ እና ስሜት ለስሜት የመስማማት ችግር እንደሌለ መረዳቱን የሚገልጥባት ቀን ናትና፡፡ ግን ምን ያደርጋል፤ ሁለቱም ይህንን በየልባቸው ያውቁታል እንጂ አልተነጋገሩም፤ ሃሳባቸውንም በሌላ መንገድ አልተለዋወጡም፡፡ በዚህ የተነሣም በችግሩ መፍቻ ቀን ዋናው ቸግር ተፈጠረ፡፡



ሁለት የትዳር ነቀርሳዎች፡- አለመቀራረብ እና አለመነጋገር፡፡ አብረው አንድ አልጋ ላይ እያደሩ፤ አብረው እየበሉ፤ አብረው እየኖሩ የማይቀራረቡ ባል እና ሚስት አሉ፡፡ አንድ አልጋ ላይ የሚተኙት አንድ አልጋ ላይ መተኛት ስላለባቸው ብቻ ነው፡ ከመጋባታቸው በፊት የነበራቸው ጉጉት እና ናፍቆት አሁን የለም፡፡ ሳይተኙ እንቅልፍ ይወስዳቸዋል፡፡ አብረው ይበላሉ፤ በአንድ ማዕድ መሆኑ፣ አንድ ጠረጲዛ ላይ መሆኑ እንጂ ያኔ በፊት ለምሳ ሲገባበዙ የነበረው ናፍቆት እና ጉጉት የላቸውም፡፡ ዝም ብሎ መብላት ብቻ፡፡



እያንዳንዷን ቀን ልዩ፣ ደስታ የሚፈጠርባት እና ከትናንት የተለየች ለማድረግ አይጥሩም፡፡ ዛሬም እንደ ትናንቱ፣ ነገም እንደ ዛሬ ነው፡፡



በስንት ልመና በስንት ጥየቃ፣

በስንት ደጅ ጥናት በስንት ጥበቃ፣

እንግዲህ ምን ቀረሽ አገባሁሽ በቃ፣



እንደተባለው ይሆንባቸዋል፡፡ አገባኋት በቃ፤ አገባሁት በቃ፤ ከንግዲህ ምን ቀረ? ብለው ያስባሉ፡፡ ሰው ተፈጥሮ አላለቀም፡፡ በየጊዜው ነው የሚፈጠረው፡፡ ፈጣሪም ሰውን እንደ ተወለደ እንዲያልቅ አላደረገውም፡፡ በየቀኑ፣ በየሰዓቱ፣ በየደቂቃው ላስተዋለው ሰው እንግዳ ፍጥረት ነው፤ አዳዲስ ነገር ይታይበታል፡፡ ይህ ግን መቀራረብን ይጠይቃል፡፡ ባል እና ሚስት ከተቀራረቡ ሳይፋቱ በየቀኑ ይጋባሉ፤ ጋብቻቸው እየታደሰ ይሄዳል፡፡ የትናንቷ ሚስት ከዛሬዋ ትለያለች፤ የዛሬው ባልም ከትናንቱ የተለየ ነው፡፡ ለውጥ፣ ዕድገት፣ ብስለት፣ አለ፡፡ መልክም ተለውጧል፡፡ ግን ቀርቦ የሚያየው ያስፈልገዋል፡፡



የዚያ ባል ችግሩ ሚስቱን አግብቷት እንጂ ቀርቧት አያውቅም ነበር፡፡ አብሯት ይኖራል እንጂ ከርሷ ጋር አይኖርም ነበር፤ ምድር በፀሐይ ዙርያ ስለምትዞር ይመሻል ይነጋል እንጂ በእነርሱ የተለየ የሕይወት ጉዞ ምክንያት አይመሽም አይነጋም፡፡ በማክሰኞ እና በረቡዕ መካከል ከስሙ በቀር በሕይወታቸው ውስጥ ልዩነት የለውም፡፡



ሌላው ችግር ደግሞ ያለ መነጋገር ነው፡፡ መነጋገር ማለት በሚያውቁት ቋንቋ ማውራት ማለት አይደለም፡፡ እርሱንማ ከብትም ሲገናኝ እምቧ እምቧ ይባባላል፡፡ ይህ ግን መነጋገር አይደለም፡፡ በየጊዜው፣ በየሰዓቱ፣ ሁለመናን መለዋወጥ ማለት ነው፡፡ ካልተነጋገሩበት የምሥራች፣ የተነጋገሩበት መርዶ ይሻላል፡፡ ካልተነጋገሩበት ፍቅር የተነጋገሩበት ጠብ ይበልጣል፡፡ ካልተነጋገሩበት ስጦታ የተነጋገሩበት ንጥቂያ ይሻላል፡፡



ባል እና ሚስቱ ባለመነጋገራቸው ችግሩን በሁለት አቅጣጫ ፈቱት፡፡ የሁለቱም ፍላጎት ችግሩን ላንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ መፍታት ነበር፡፡ የሁለቱም ፍላጎት ፍቺ የሚባለውን ነገር ላለማየት ነበር፡፡ የሁለቱም ፍላጎት ሠላሳኛዋን ቀን መገላገል ነበር፡፡ ነገር ግን ባለ መነጋገር ምክንያት በሁለት አቅጣጫ ሆነ፡፡ እርሷ ሞትን መረጠች፤ እርሱ ደግሞ ይቅርታን መረጠ፡፡ ችግሩ የመጣው በዚህ ጉዳይ ላለመነጋገር ሲወስኑ ነው፡፡ እርሷ በጉዳዩ ትጨነቃለች፤ ለምን ይሆን ከኔ መለየት የፈለገው? የሚለው ጥያቄ ያሳስባት ነበር፡፡ በሃሳብ ብዛትም እየከሳች ሄዳ ነበር፡፡ ለዚህም ነበር በየቀኑ ሲያቅፋት ትቀልለው የነበረው፡፡ እርሱ ግን መቅለሏን እንኳን ለመጠየቅ ፈራ፡፡ እርሱ ከራሱ ጋር እንጂ ከእርሷ ጋር አይነጋገርም ነበር፡፡



እናም አንዳንድ ጊዜ አስፈላጊ ቢሆንም እንኳ፤ በትዳር ውስጥ ግን ዝምታ ወርቅ አይደለም፡፡







ከዲዳለ





እርሶስ ምን ይላሉ?

3 comments:

Anonymous said...

ተመስገን ! ይሄ ብሎግ ከተጀመረ ዛሬ ገና ቁምነገር ያለበት ጽሑፍ አነበብኩ፡፡ጀምሬም ጨረስኩት፡፡ እስከዛሬ ግን እጀምረውና ልክ የጭቃ ጅራፉን በሰው ላይ ለመመረግ ሲያነሣ ጌታ ሆይ ይህን የተጠናወተውን የስድብ ጋኔን አርቅለት ብዬ አቋርጠዋለሁ፡፡ ዛሬ ግን ስለትዳር ቁምነገር አግንቼበታለሁና ጸሐፊውን አመሰግናለሁ፡፡

Anonymous said...

እኚ ከመጀመሪያ ላይ አስተያየት የሰጡት ጽሁፉ የገባቸው አልመሰለኝም። ችግሩ ከወዲያ ወገን ስለሆኑ እስከዛሬ የቀረቡትን ሁሉ እስከመጨረሻው አንብበው የራሳቸውን ጥናት ማድረግና ግንዛቤ መውሰድ የማያውቁ ጥሬ ይሆናሉ የሚል መደምደሚያ የሚገባቸው መሰለኝ። ምሳሌነቱን አልተረዱትምና ትንሽ ላስጨብጦት እወዳልሁ ታሪኩ የሚዛመደው አንድ ትውልድ ሁገር ፣ አንድ ቁዋንቃ የሚናገር ፣ አንድ አይነት በአልና እምነት ያለው ህብረተሰብ እንዴት በአንድ ላይ አብሮ ማምለክ ተሳነው? የእውነት ወይስ የሀሰት እምነት የያዘው? መጨረሻውስ? እስቲ ይለውጡ ከሆነ ዳዴ ወፌ ቆመች እንበልዎ።

Anonymous said...

Greeting to all of you, and thanks for Dallaseotc bloggers’, for your service.

I have here picked the following from your piece.

ባል እና ሚስቱ ባለመነጋገራቸው ችግሩን በሁለት አቅጣጫ ፈቱት፡፡ የሁለቱም ፍላጎት ችግሩን ላንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ መፍታት ነበር፡፡ የሁለቱም ፍላጎት ፍቺ የሚባለውን ነገር ላለማየት ነበር፡፡ የሁለቱም ፍላጎት ሠላሳኛዋን ቀን መገላገል ነበር፡፡ ነገር ግን ባለ መነጋገር ምክንያት በሁለት አቅጣጫ ሆነ፡፡ እርሷ ሞትን መረጠች፤ እርሱ ደግሞ ይቅርታን መረጠ፡፡ ችግሩ የመጣው በዚህ ጉዳይ ላለመነጋገር ሲወስኑ ነው፡፡ እርሷ በጉዳዩ ትጨነቃለች፤ ለምን ይሆን ከኔ መለየት የፈለገው? የሚለው ጥያቄ ያሳስባት ነበር፡፡ በሃሳብ ብዛትም እየከሳች ሄዳ ነበር፡፡ ለዚህም ነበር በየቀኑ ሲያቅፋት ትቀልለው የነበረው፡፡ እርሱ ግን መቅለሏን እንኳን ለመጠየቅ ፈራ፡፡ እርሱ ከራሱ ጋር እንጂ ከእርሷ ጋር አይነጋገርም ነበር፡፡ this has a wise message for acknowledge one it’s self. It is very powerful statement.

I want to relate to the past, present and the future for our Church. The root cause of the problem in our Church was started back when the Eretria become independence. Time after time, the same group of individuals become in the Leadership (Board) and their ability to tackle and resolved the issues failed, on the other side they want their personality and their names become important than the Faith which made them be part of the problem. They love to drag the issues under the carpet. Since the group called Maiheber Kidusan reaching to be elected to the Board, become employee in the administration as well as a spiritual teacher, and the uncounted fund believed was embezzled by the Board Members. In addition the spiritual employees as a Priest was part of most the problem because they have the position to educate the follower and as their duty to council, instead they want to have control the power or breakaway and create their own Church. These so called Priests were put their spiritual influence to become a personal spiritual father ( የንስሀ አባት / የነፍስ አባት), particularly putting more pressure on the wives to control the husband. Because of such behave of the Priest resulted in disagreement in the Marriage as well Husband and Wife going to different Church. What more trouble is such odd relationship in the Household lead to seek to look other Faith? We become witness that some followers choose not to go to a Church as well as their kids start going to the Protestant Church. A good friend of mine takes his kids to the Greek’s Church because of what is going on in our Church. Let us find one Priest from this Church reached to the level of retirement with dignity.

Few followers time to time become a statistic and left with such Priest. Other they want power for themselves than looking to their own faith, they took the road to the Court. They pertained they are for religion that they did, but the truth is for power. They can not to tell us one single reason they have where the Orthodox Religion is broken and the Faith is destroyed in our Church, just want control and embezzled the Church funds. These individuals are not a member for this Church and if they were they could utilized the BY-Law. In general they are not what they claim the followers of the Faith. As it was written in Amharic above, they want destroy and kills the true followers, they are enemy of GOD.

Salomon from Dallas